
የዳያስፖራ ኢንቨስትመንት ፎረም እየተካሄደ ነዉ
የአዲስ አበባ፣ ጥር 3፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተቀብለው ወደ አገር ቤት የመጡ የዳያስፖራ አባላት ኢንቨስትመንት ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነዉ።ዳያስፖራው በኢትዮጵያ የሚገኙ የኢንቨስትመንት አማራጮችንና እድሎችን በመጠቀም መዋዕለ ንዋዩን በማፍሰስ ለአገሩ ምጣኔ ሐብትና ብልጽግና አስተዋጽኦ ማድረግ የሚችልበትን ዕድል ለማመላከት ያለመ ፎረም መሆኑን የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሌሊሴ ነሜ ገልጸዋል።ዳያስፖራው ወደ መጣበት ሲመለስ በኢትዮጵያ ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማስተዋወቅ አምባሳደር እንዲሆን ኮሚሽነሯ ጠይቀዋል።
የውጪጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን “ፖለቲካን ማሸነፍ የሚቻለው የኢኮኖሚ ፈተናዎችን ማሸነፍ ሲቻል ነው” ሲሉ ገልጸዋል።በመሆኑም ዳያስፖራው ለአገሩ በፖለቲካው እያደረገ ያለውን አጋርነት በኢንቨስትመንት በመሳተፍ ለኢትዮጵያ እድገት አስተዋፅኦ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።በመድረኩ 800 የሚሆኑ የዳያስፖራ አባላት የተገኙ ሲሆን፥ በጤናው እና ሌሎች ዘርፎች ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች ቀርበውላቸዋልም ነው የተባለው።በፎረሙ ላይ የክልል የኢንቨስትመንት ቢሮዎች ያላቸውን የኢንቨስትመንት አማራጮች፣ ባንኮችና ሪል ስቴት አልሚዎች አማራጮቻቸውን ይዘው እንደቀረቡም ተገልጿል።እስከ መጪው አርብ ድረስ የሚቆይ የኢንቨስትመንት አማራጮችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽንም መዘጋጀቱን ኢዜአ ዘግቧል።
የዳያስፖራ ኢንቨስትመንት ፎረም እየተካሄደ ነዉ